
13/04/2025
" ጤና ሚኒስቴር ' አጽድቄዋለሁ ' የሚለው አዋጅ የጤና ባለሞያዎችን ችግር የሚፈታ ነው ይላል ነገር ግን ችግሮቻችን እነኚህ ብቻ አይደሉም " - ሃኪም
➡️ " አዋጁ የጤና ባለሞያዎችን የረጅም ጊዜ ጥያቄ የሚመልስ ነው " - ጤና ሚኒስቴር
የጤና ባለሞያዎች " ለዘመናት እየጠየቅናቸው ያሉ በጤናው ዘርፍ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮቻችን ይፈቱ" ሲሉ ድምጻቸውን በተለያየ መንገድ በዘመቻ እያሰሙ ናቸው።
በርካታ ባለሙያዎችም ጥያቄያቸውን እና ቅሬታቸውን ለቲክቫህ ኢትዮጵያ አቅርበዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ የጤና ባለሙያዎቹ በተለያዩ መንገዶች እያካሄዱ የሚገኙትን ዘመቻ ለመከታተል ባደረገው ጥረት በርካታ ባለሙያዎች በተናጠል እንዲሁም አንዳንድ የሞያ ማህበራት ዘመቻውን እያስተጋቡ መሆኑን ለማስተዋል ችሏል።
10 ነጥቦችን ይዞ የተነሳው ዘመቻ ፦
- የኢኮኖሚ፣
- የትርፍ ሰዓት ክፍያ፣
- የሃኪሞች የሥራ ቦታ ደህንነት ፣
- የቤት እና የትራንስፖርት አቅርቦት፣
- አግባብነት ያለው ወቅታዊ የሥራ ክፍያ
- ለአለም አቀፍ የሥራ ገበያ የሚወዳደሩበት የብቃት መመዘኛ የፈተና ማዕከላት በሃገር ውስጥ እንዲቋቋሙ ይጠይቃል።
ንቅናቄው የኢትዮጵያ የህክምና ማህበር ድጋፍ ያለው ስለመሆኑ ለማረጋገጥ ለማህበሩ ፕሬዝዳንት ፣ ስራ አስፈጻሚዎች እና የህዝብ ግንኙነት ክፍል ተደጋጋሚ ሙከራ ብናደርግም ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆኑም።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ የማህበሩ አባል ከሆኑ እና ስሜ አይጠቀስ ብለው ከጠየቁ የጤና ባለሞያ ንቅናቄው የማህበሩ ሙሉ ድጋፍ ያለው ስለመሆኑ አረጋግጠዋል።
" ማህበሩ ከዚህ በፊት ሲያነሳ የነበራቸው በርካታ ጥያቄዎች ነበሩ ባለመመለሳቸው ምክንያት ድጋሚ ጥያቄውን በማንሳት ለጤና ሚኒስቴርም ደብዳቤ እንሚያስገቡ እና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮም እየተዘጋጀ ያለ ደብዳቤ መኖሩን መረጃው አለኝ " ብለዋል።
የጤና ባለሞያና የማህበሩ አባል በዝርዝር ባነሱት ሃሳብ ምን አሉ ?
" የንቅናቄው የመጀመሪያ አላማ የጤና ባለሞያዎችን መብት ማረጋገጥ ነው።
መብት ስንል ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ መብት ሊሆን ይችላል በዋናነት ኢኮኖሚያ ያለብን ጫና መስተካከል አለበት።
የአንድ ሃኪም የሚከፈለው ደሞዝ እና የሚኖርበት ሁኔታ ሲታይ በጣም አሳፋሪ ነው።
እየተራበ የሚያገለግልበት ሰዓት ታሳቢ ተደርጎ ፣ምን ያህል ድካም እንዳለበት እና ምን ያህል ሰዓት እንደሚሰራ ታሳቢ ተደርጎ ሊከፈል ከሚገባው ጋር አይመጣጠንም።
የትኛውም ሆስፒታል የሚሰራ ሃኪም ሳይከፍል መታከም አይችልም እንደማንኛውም ህብረተሰን ካርድ አውጥቶ እና ከፍሎ ነው የሚታከመው ይህ መሆን የለበትም በሚያገለግልበት ሆስፒታል ነጻ የህክምና አገልግሎት ሊመቻችለት ይገባል።
ጤና ሚኒስቴር ' አጽድቄዋለሁ ' የሚለው አዋጅ የጤና ባለሞያዎችን ችግር የሚፈታ ነው ይላል ነገር ችግሮቻችን እነኚህ ብቻ አይደሉም በአንድ በኩል ብቻ ችግሩን ለመፍታት የሚደረገው ጥረት አመርቂ አይደለም ከዚህ ቀደምም የተነሱ ጥያቄዎች አሉ አንዱን ክንፍ ብቻ ፈትተህ ሙሉ በሙሉ ችግሮቹ ተፈተዋል ብለህ የምትናገረው አይደለም።
የእኛ ጥያቄ ችግሮቹ በሙሉ ይታዩ ነው ከችግሮቹ መካከል አንድ ነጠላ ነገር ብቻ አውጥተህ ይኸው ችግራቹን ፈትተናል ችግር የለም ተብሎ ለማድበስበስ የሚኬደው ጥረት ተገቢ አይደለም " ብለዋል።
የጤና ሚኒስቴር ከሰሞኑ በማህበራዊ ትስስር ገጹ ባጋራው መልዕክት በቅርቡ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 13ኛ መደበኛ ገባኤ ላይ የጸደቀው " የጤና አገልግሎት አስተዳደር እና ቁጥጥር አዋጅ ቁጥር 1362/2017 " የጤና ባለሞያዎችን የረጅም ጊዜ ጥያቄ የሚመልስ ነው ብሏል።