ፍኖተ ማዕምር የስነ-ልቦና አገልግሎት/Finote Maemr Psychological service

  • Home
  • Ethiopia
  • Addis Ababa
  • ፍኖተ ማዕምር የስነ-ልቦና አገልግሎት/Finote Maemr Psychological service

ፍኖተ ማዕምር የስነ-ልቦና አገልግሎት/Finote Maemr Psychological service Psychological Counseling
Life Skills Training

22/10/2023

ለምን ህይወታችንን በበዛ ግዴታ እንጨምቀዋለን?

በምርጫችን አልመጣንም፤ በምርጫችንም አንሔድም።

ህይወት ያለው ሁሉ በመኖር ትግል ውስጥ ማለፉ ጤናማና የሚጠበቅ የተፈጥሮ ሒደት ነው። በዚህ መነሻ ካየነው ራስን ማጥፍት ፀረ- ተፈጥሮ ተግባር ይሆናል።

ተፈጥሮ ያዘጋጀችን ያለንን አቅም ተጠቅመን ለመኖር ነው ብለን ከተነሳን ራስን ማጥፋት የተፈጥሮን ፍሰት ማቋረጥ፣ ጉዞዋን ማኮላሸት ነው። ይህ ማለት ራሳቸውን የሚያጠፉ ሰዎች ተወቃሽ ናቸው ማለቴ አይደለም። አልችል ብለው እንጂ ሲሆንማ መኖር ማን ይጠላል?

አብዛኛዎቻችን የግድ ይህ መሆን አለበት፣ የግድ ይህን ማሳካት አለብኝ፣ ደስተኛ ለመሆን የግድ ይህ መሟላት አለበት የሚሉና መሰል የፍፅምና አስተሳሰቦች ደስታችንን ያደፈርሱታል። ገዢ አስተሳሰቦች ሲሆኑም ወደ ከፋ ቀውስ ሊገፉን ይችላሉ።

ራስን ማጥፋት የደሀ እጣ የሚመስላቸው ሰዎች አሉ። እውነታው ራስን ማጥፋት ከቁስ ድህነት ይልቅ ከተስፋ ድህነት ጋር በቀጥታ ይያያዛል።የምንኖርበት ቁስ ማግኜት አስፈላጊ ጉዳይ ቢሆንም ትርጉም ያለው ህይወት ለመኖር ዋስትና አይደለም። መኖሪያችንን ሰርተንም ሰርቀንም ልናሳካው እንችል ይሆናል።የምንኖርለትን ምክንያት ፈልገን ማግኜት ሌሎች የሚሰጡን ፣ እንደ ሀብት ቤተሰብ የሚያወርሰን ወይም ከሰማይ የሚወርድልን መና አይደለም። ይልቁንም ከህይወት ውጣ ውረድ ፈልቅቀን የምናወጣው የምርጫችን ውጤት እንጂ።

በናዚዎች ጭካኔ እንደ እኤአ ከ1942-1945 ባሉት አመታት በተለያዩ የማጎሪያ ጣቢያዎች የከፋ ስቃይን ያሳለፈው ቪክቶር ፍራንክል (ዶር) በእያንዳንዱ ህይወታችን ውስጥ ምርጫ እና አንፃራዊ ነፃነት አለን ብሎ ያምናል። በማጎሪያ ካምፕ ውስጥ ሳይቀር አጋቾች ሊቆጣጠሩት የማይቻላቸው መንፈሳዊ ነፃነት አለን ይለናል።

መከራ እና አስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ የህይወትን ትርጉም ፈልቅቀን የምንወጣበትን የተፈተነ ልምድ Man's search for meaning በሚል መፅሐፍ ከተቦልን አልፏል።የExistentialism አቀንቃኞች በአግባቡ የሚኖር ህይወት ስለሞት ካለ ጥልቅ መረዳት ይመነጫል ይሉናል። የመኖር ዋናው ምክንያት ደግሞ ከስቃያችን ፈልቅቀን የምንቀዳጀው የህይወት ትርጉም ነው። የህይወት ትርጉሙ ሲጠፋብን የኦናነት ስሜት (Sense of vacuum) ይፈጠራል። በጊዜ ካልተፈታ በተራው ወደራስን ማጥፋት ይመራናል የሚል እይታ አላቸው።

#ስለ ራስን ማጥፋት አንዳንድ ነገሮች

ራስን ማጥፋት ድንገቴ ጉዳይ አይደለም። ብዙ ጊዜ ታስቦበት የሚፈፀም እንጅ። አብዛኞቹ የዚህ ችግር ሰላባዎች የታወቀም ይሁን ባልታወቀ የስነልቦና ህመም የሚሰቃዩ ናቸው። ራሳቸውን ከሚያጠፉት ይልቅ ራስን በማጥፋት ስሜት የሚሰቃዩት በበዙ እጥፍ ይበልጣሉ። ስለሆነም የዚህ ስሜት ተጠቂዎች ሌሎች እንዲረዱላቸው እና እንዲያውቁላቸው ተደጋጋሚ ጥረቶች ያደርጋሉ።

ራስን ማጥፋት ለመኖር አቅም የማጣት ውጤት ነው። ይህ ስሜት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጠነከረ የሚመጣ ሲሆን የተግባር ምልክቶችም አሉት።
1. ተደጋጋሚ ስለራስ አሉታዊ ንግግር (Negative self talk)
እኔ ለማንም አልጠቅምም፣ አልረባም፣ ዋጋ የለኝም፣ የቤተሰብ ሸክም ነኝ እና መሠል ሀሳቦች
2. ራስን መበዝበዝ (Self distractive behavior)
ራስን በሚጎዱ ድርጊቶች መዘፈቅ፣ ለህይወት የበዛ ደንታ ቢስነት፣ በአልኮል-እፅ መዘፈቅ፣ በተደጋጋሚ ጥንቃቄ የጎደለው የግብረስጋ ግንኙነት መሳተፍ፣ ምክንያት አልባ አደጋዎችን መጋፈጥ
3. ረዘም ላለ ጊዜ በአሉታዊ ስሜቶች መሰቃየት -ከፍተኛ ፀፀት፣ ድባቴ፣ ሀዘን፣ ትርጉም አልባነት፣ የመነጠል ስሜት ወዘተ

ተጠቂዎች እነዚህን ካለፉ በኋላ ወደ መጨረሻ ደረጃ ሲደርሱ ስለሞት በተደጋጋሚ ማውራት፣ ከህይወት እረፍት እንደሚፈልጉ መለፈፍ፣ ራስን የማጥፊያ አማራጮችን ማማተር እና የስንብት/ኑዛዜ መልዕክቶች መተው የተለመዱ ናቸው።

# ምን አይነት እገዛ ይፈልጋሉ?
እመለስበታለሁ

10/10/2023

የአዕምሮ ጤና ጉዳይ

ልጅ ሆኜ ከማስታውሳቸው መፈክሮች መካከል ...'ያለ አዕምሮ ጤና ጤና የለም' የሚል ይገኝበታል። በዛሬዋ ዕለት የአዕምሮ ጤና ጉዳይ በአለማቀፍ ደረጃ "Mental Health is a universal human right" በሚል ታስቦ ውሏል።

በሀገራችን የአዕምሮ ጤና ጉዳይ የተዘነጋ ጉዳይ ነው ለማለት ያስደፍራል። የችግሩን ጥልቀትና ስፋት ካጤንን ደግሞ አንገታችን ድረስ ውጦናል።እግር ከወርች ጠፍሮ ይዞናል። ለምሳሌ ከአምስት ዓመት በፊት ብሔራዊ ስታስቲክስ ኤጀንሲ ባወጣው የዳሰሳ ጥናት ኢትዮጵያ ውስጥ የአዕምሮ ጤና ችግር 27.4% መድረሱን አርድቶናል።

በቅርቡ የአለም ጤና ድርጅት ከጅማ ዩኒቨርስቲ ጋር ባደረገው የዳሰሳ ጥናት ኢትዮጵያ ውስጥ የድብርት ተጠቂዎች ብቻ ከዘጠኝ ሚሊዮን ይበልጣሉ ይለናል።ሌሎች ብዙ አይነት የአዕምሮ ጤና እክሎች ሲደማመሩ በጣም አስደንጋጭ አሀዝ ነው።እንግዲህ ባለፉት አምስት ዓመታት ያለፍንባቸውን ሰቆቃዎች ማለትም የእርስበርስ ጦርነት፣ ማንነት ተኮር ጥቃት፣ፆታዊ ጥቃት፣መፈናቀል፣ የኑሮ ውድነት ወዘተ ሲጨመሩ ይህ አሀዝ ብዙ ይጨምራል።

አሁን ለገባንበት ሀገራዊ ቀውስ የአዕምሮ ጤና እክል ድርሻው ከፍተኛ እንደሚሆን አምናለሁ። በየተቋማቱ የአዕምሮ ጤና እክል ባለባቸው ሰዎች ላለመመራታችን ምን ዋስትና አለን?
ከላይ የተጠቀሰውን አሀዝ ወስደን ግርድፍ ግምት ብናስቀምጥ ከ100 ሰዎች ከ27 በላይ የሚሆኑት የችግሩ ሰለባ ናቸው እንደማለት ነው። ከ100 የተቋማት ሀላፊዎች መካከል ከ27 በላይ የሚሆኑት የአዕምሮ ጤና እክል ያለባቸው ቢሆኑ የሚፈጠረውን ቀውስ አስቡት ።

በቀደመ ጊዜ መሪዎችን እንደ ወንፊት ሆነው የሚያበጥሩ ባህላዊ ስርዓቶች የነበሩን ቢሆንም ከቅርብ አስርት ዓመታት ወዲህ ግን በጥላቻ የሰከሩ፣ ስሜታቸውን መቆጣጠር የተሳናቸው፣ ለራሳቸውም ሆነ ለህዝብ ደንታ የሌላቸው መደዴ ተሳዳቢዎችን የተቋማት መሪዎች ሆነው ማየት የተለመደ ሆኗል። እንደ Anti social personality disorder አይነት የስዕብና ውጥንቅጥ ተጠቂዎች ሰላም ሲሆን ደስ የማይላቸው "ጭር ሲል አልወድም" የሆኑ ሰዎች እንዳሉ ስንቶቻችን እናውቃለን? የዚህ ተጠቂዎች በሀላፊነት ላይ ሲሆኑ ምን ሊከሰት እንደሚችል ማሰቡ ራሱ ከባድ ነው።

ብዙ ቀጣሪ ድርጅቶች ሰራተኞቻቸውን ለመቅጠር አንዱ ቅድመ ሁኔታ የጤና ምርመራ ውጤት ነው። ይህ ግን አካላዊ የጤና ምርመራን እንጂ አዕምሯዊ ጤናን አይመለከትም። አዕምሯዊ ጤንነት በቀላሉ የማይለይ ረቂቅ እና ድብቅ ነው። በመሆኑም ተጠቂዎች ራሳቸው ከችግሩ ጋር መኖራቸውን ላያውቁት ይችላሉ።

የአዕምሮ ጤና ችግር መኖርን አመላካች ሶስት አንኳር ጉዳዮች መካከል ምክንያት አልቦ አፈንጋጭነት፣ ተደጋጋሚ የሆነ የሚረብሽ የስሜት (አሉታዊ ስሜቶችን)ማስተናገድ እና ወጥነት ያለው የስራ ህይወትን፣ ማህበራዊ ህይወትን እና ግለሰባዊ ህይወትን የሚጎዳ ፀባይ መላበስ ዋና ዋናዎቹ ናቸው። እነዚህ ጠቋሚ ምልክቶች መኖራቸው ብቻ ለመፈረጅ አያስችልም። ሌሎች ምርመራዎችን እና ነባራዊ ሁኔታዎችን ያስገባ ሙያዊ እይታ ይፈልጋል።

እናም በሀገራችን ያለው ማህበራዊ ትስስር እየተበጣጠሰ፣ ሀይማኖቶች ጉልበታቸው እየዛለ፣ የአኗኗር ዘይቤያችንን በግድ የሚያስቀይር ከተሜነት በተስፋፋ ወዘተ ችግሩ እየሰፋ መሔዱ ከግምት በላይ ነው። ችግሩን በትክክል መረዳት ለመፍትሔው ያዘጋጃል።

ለወደፊት ለሁሉ እንኳን ማድረግ ባንችል በብዙ ሰዎች ህይወት ተፅዕኖ የሚያሳድሩ ወሳኝ ሀላፊነት የሚሰጣቸው ሰዎች እንደ አካላዊ ጤና ምርመራ ሁሉ የአዕምሮ ጤናማነት ማረጋገጫ ስርዓት መዘርጋት ጥሩ ይሆናል።

Address

Addis Ababa

Telephone

+251910818783

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ፍኖተ ማዕምር የስነ-ልቦና አገልግሎት/Finote Maemr Psychological service posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Practice

Send a message to ፍኖተ ማዕምር የስነ-ልቦና አገልግሎት/Finote Maemr Psychological service:

Share

Share on Facebook Share on Twitter Share on LinkedIn
Share on Pinterest Share on Reddit Share via Email
Share on WhatsApp Share on Instagram Share on Telegram

Category