17/11/2025
" እስካሁን ሌላ ቦታ (ከጂንካ ውጭ) የተገኘ ኬዝ የለም " - ጤና ሚኒስቴር
➡️ " ምልክት በታየበት አካባቢ ንክኪ የነበራቸው 129 ሰዎች እራሳቸውን ለይተው እንዲያስቀምጡ መልዕክት ተነግሯቸዋል "
የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ እስካሁን ተጠርጥሮ በለይቶ ማቆያ ያለ ታካሚ አለመኖሩን ተናግረዋል።
ዶ/ር መቅደስ በማርበርግ ቫይረስ በሽታ ተጠርጥረው የላብራቶሪ ምርመራ ከተደረገላቸው 17 ሰዎች 14ቱ ሰዎች ኔጌቲቭ (ነጻ) መሆናቸውን ገልጸዋል።
" ምልክት በታየበት አካባቢ ንክኪ የነበራቸው 129 ሰዎች እራሳቸውን ለይተው እንዲያስቀምጡ መልዕክት ተነግሯቸዋል " ያሉት ሚኒስትሯ " ያ ግን በጣም በሩመር ያለውንም ጨምረን ነው፣ ቀጥታ ንኪኪ ያላቸው ተብሎም የሚመዘገብ አይደለም፣ ይህንንም እያጣራን ነው " ሲሉ ተናግረዋል።
በዚህ በሽታ ከጂንካ ውጪ ምልክት የታየበት አከባቢ አለ ?
የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ ፤ የማርበርግ ቫይረስ ከተገኘበት ከጂንካ የወጡ ከቫይረሱ ጋር ንክኪ አላቸው የተባሉ ሰዎች እንደነበሩ አንስተዋል።
" ከእነሱ ጋር ንክኪ ያላቸው ሰዎችን የመለየት ስራ እየሰራን ነው። እስካሁን ሌላ ቦታ የተገኘ ኬዝ የለም " ብለዋል።
" ምልክት አለባቸው ብለን የምንጠረጥራቸውን በሙሉ ምርመራ አድርገናል። ሁሌም እንደዚህ አይነት ቫይረሶች ሲከሰቱ የምንቆጥረው ኬዙ ከተገኘበት ከክልሉ ነው ፤ ያለበለዚያ የማደናገጥ ሥራ ይሆናል " ሲሉ በሌላ አከባቢ ኬዙ አለመገኘቱን ገልጸዋል።
" ከክልሉ (ደቡብ ኢትዮጵያ) ውጪ ሌላ ፖዘቲቭ ኬዝ አላየንም። ወረርሽኙን በአጭር ጊዜ መቆጣጠር ነው ዋናው አላማችን ነው " ያሉት።
" በሽታው በንክኪ የሚተላለፍ ነው፣ የበሽታው ምልክት ካለባቸው ሰዎች ጋር መነካካት አያስፈልግም። ሁል ጊዜም ካላስፈላጊ ንክኪ መቆጠብ አለብን " ሲሉ አሳስበዋል።
ለዚህ በሽታ መድሀኒቱ ምንድን ነው ?
" ለዚህ በሽታ የመጀመሪያ መድሃኒቱ መከላከል ነው " ያሉት ሚኒስትሯ፥ " የበሽታው ምልክት በሚኖርበት ጊዜ በተለይ ፦
- ትውከት፣
- ማስቀመጥ፣
- ትኩሳት እና እንደዚህ አይነት ነገሮች በሚኖሩበት ጊዜ Supportive የምንላቸውን ህክምናዎች ይሰጣሉ " ብለዋል።
በዓለም አቀፍ ደረጃ ለዚህ ቫይረስ ይሄ ነው መድሀኒቱ ተብሎ የተቀመጠ ነገር አለመኖሩን ጠቅሰው፥ " ነገር ግን ሌሎች ሀገሮች የሞከሯቸውን እንዲሁም በሙከራ ላይ ያሉ መድሃኒቶችን ወደ እኛም ሀገር ማምጣት የሚቻልበትን ሁኔታ ጀምረናል " ብለዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
አዲስ አበባ