14/03/2026
ኤካ ኮተቤ ሆስፒታል ለአመራር ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና ሰጠ!
ቢሾፍቱ — ኤካ ኮተቤ ሆስፒታል በቅርቡ በሆስፒታሉ አዲስ መዋቅር ተወዳድረው ለአመራርነት የተመረጡ ባለሙያዎችን ክህሎት የሚያሳድግና ተቋማዊ ሪፎርሙን የሚያፋጥን ጥልቅ ስልጠና በቢሾፍቱ ከተማ ሰጠ።
የስልጠናውን መርሃ-ግብር በንግግር የከፈቱት የሆስፒታሉ ቺፍ ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ዶ/ር መገርሳ አለሙ እንደገለጹት፤ አዲሱ መዋቅር ውጤታማ እንዲሆን አመራሩ በዘመናዊ የሥራ አመራር ዕውቀት ራሱን ማብቃት ይኖርበታል ብለዋል
ዳይሬክተሩ አክለውም፣ አመራሮች የአሰራር ስልቶችን በመቀየስና የአገልግሎት አሰጣጥ ሂደቶችን በማቀላጠፍ ለታካሚዎች ጥራት ያለውና ቀልጣፋ ግልጋሎት እንዲሰጡ አሳስበዋል።
ይህ ስልጠና በዋናነት ትኩረት ያደረገው በቀጣይ በሚከናወኑ የሆስፒታሉ የሥራ እንቅስቃሴዎች ላይ የጥራት ደረጃን ለማዘመን በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ ነው።
የስራ ሀላፊዎች የስራ መዘርዝርን በመውሰድ ተፈጻሚ እንዲያደርጉ ዘመናዊ የሥራ ስልቶችን መዘርጋት፣ ግልጽ የሆኑ የተጠያቂነት መመሪያዎችን ተግባራዊ ማድረግ፣ ሠራተኞችን የሚያበረታቱ የማትጊያ መመሪያዎችን ሥራ ላይ ማዋል የሚሉ ነጥቦች በስልጠናው በስፋት ተዳስሰዋል።
እነዚህ መመሪያዎች ተቋሙ የላቀ፣ የተቀላጠፈና በውጤት ሊለካ የሚችል የሥራ ባህል እንዲገነባ ፋይዳቸው የጎላ መሆኑ ተመላክቷል።
በስልጠናው ላይ የተሳተፉ የየክፍሉ ዳይሬክተሮች እና የዴስክ ኃላፊዎች በስራቸው ለሚገኙ ባለሙያዎች ስራን በቁጥርና በጊዜ ለክቶ የመስጠት፣ የሥራ አፈፃፀምን ተከታትሎ የመረከብ እንዲሁም በትጋት ለሚሠሩ ባለሙያዎች ተገቢውን ዕውቅና የመስጠት ክህሎታቸውን የሚያሳድጉ የሥልጠና ሞጁሎች ቀርበውላቸዋል።
በተጨማሪም በሥራ ሂደት ላይ የሚያጋጥሙ ክፍተቶችን አስቀድሞ በመለየትና መፍትሔ በመስጠት፣ የሆስፒታሉን ራዕይ ዳር ለማድረስ የሚያስችል "ተቋማዊ የአሠራር ሮድ ማፕ" ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል።
ሰልጣኞቹ በቆይታቸው የቀሰሟቸውን ዕውቀቶች በሥራ ላይ እንዴት ማዋል እንደሚችሉ የሚያሳዩ ዕቅዶችን አቅርበው የጋራ መግባባት ላይ ተደርሷል።
"የአገልግሎት ጥራት አርማችን"