20/02/2026
የጎንደር አይራ ጠቅላላ ሆስፒታል እና የጎንደር ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በሁሉም አይነት ህክምና ዙሪያ በጋራ ለመስራት ስምምነት ተፈራረሙ
*
የጎንደር አይራ ጠቅላላ ሆስፒታል እና የጎንደር ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በጠቅላላ ቀዶ ጥገና ፣በአጥንት ስብራት ህክምና ፣በማህፀንና ፅንስ ፣ በህፃናት እና በሌሎች የህክምና ዘርፎች ላይ በጋራ ለመስራት የሚያስችል የጋራ ስምምነት ዛሬ የካቲት 13/2018 ዓ.ም በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንንት ጽ/ቤት ተፈራርመዋል።
በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የጎንደር አይራ ጠቅላላ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ አቶ ገ/ዮሀንስ የሺነህ ፣ የጎንደር አይራ ጠቅላላ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር ዶ/ር ሳሙኤል አጥቃቸዉ፣ የጎንደር ከተማ አስተዳደር ጤና ምሪያ ሀላፊና የሆስፒታላችን የቦርድ አመራር አቶ ሰዒድ የሻዉ እና የሆስፒታል የማኔጅመንት አባላት እንዲሁም የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር አስራት አፀደወይን፣የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ እና አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ዋና ስራ አስፈፃሚ ዶ/ር ጌታው ብርሀን፣ የሆስፒታሉ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተው በስምምነት ሰነዱ ዙሪያ ሰፊ ውይይት አድርገዋል።
ስምምነቱ በተለይ የቀዶ ጥገና (Back Log) ቁጥሩ ከፍተኛ ሲሆን ቀጠሮ ተሰጥቷቸው ለረጅም ጊዜ በወረፋ ላይ የሚገኙ ታካሚዎችን ምልልስ በመቀነስ፣ ፈጣን የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ ማስቻል ሲሆን፣ በተለይ ለበርካታ ወራት የቀዶ ጥገና ህክምናዎችን የሚጠብቁ ታካሚዎችን ቁጥር ሆስፒታላችንን በመጠቀም በከፍተኛ ሁኔታ በመቀነስ ታካሚወች ወረፋ ከመጠበቅ ይልቅ ቶሎ ህክምና እንዲያገኙ ያለመ ስለመሆኑ በመርሀ- ግብሩ ተገልጿል። በተጨማሪም ታካሚዎች በህመማቸው ላይ ተጨማሪ እንግልትና የኢኮኖሚ ጫና ሳይደርስባቸው ጥራት ያለው ህክምና እንዲያገኙ ለማድረግ የሚያሰችል መሆኑ በስምምነቱ ተጠቅሷል።
ሁለቱ ሆስፒታሎች ከዚህ ቀደምም በሰው ኃይል እና በህክምና ቁሳቁስ ግብዓቶች ላይ የመዋዋስና የመረዳዳት ስራዎችን ሲሰሩ የቆዩ ሲሆን፣ የዛሬው ስምምነት ይህንን ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግርና ህጋዊ ማዕቀፍ የያዘ እንደሆነ ከቀረበው ገለፃ ለመረዳት ተችሏል።
የታካሚዎችን እርካታ ይበልጥ ለማሳደግ ከሁለቱ ሆስፒታሎች ስምምነት ጎን ለጎን ጤና ጣቢያዎችን የመደገፍ፣የማብቃትና የማጠናከር ስራዎች እንደሚሰሩ ተጠቁሟል። ይህም ህብረተሰቡ በአቅራቢያው በሚገኙ የጤና ተቋማት ተገቢውን አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላል ተብሏል።
የሆስፒታሉ ህዝብ ግንኙነት
የካቲት 13/2018 ዓ. ም