16/04/2026
የበልግ ዝናብን ተከትሎ የሚከሰቱ ወረርሽኞችን ለመከላከል የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛል :- ዶ/ር አብዲ አሚን
************************************
የበልግ ዝናብ ተከትሎ ሊከሰቱ የሚችሉ የውኃ ወለድ ወረርሽኝንና የወባ በሽታን ለመከላከል አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የሐረሪ ክልል ጤና ጥበቃ ቢሮ አስታወቀ።
የቢሮው ኃላፊ ዶክተር አብዲ አሚን እንደገለጹት፤ የዝናብ ወቅት ለትንኝ መራባትና ለውኃ መበከል አመቺ ሁኔታን ስለሚፈጥር፣ ቢሮው በሽታዎቹ ከመከሰታቸው በፊት የመከላከል ሥራ ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ ይገኛል።
በዚህም መሠረት በሁሉም ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች ወባን ለመመርመርና ለማከም የሚያገለግሉ መድኃኒቶችና የላቦራቶሪ ግብዓቶች በበቂ ሁኔታ እንዲሟሉ መደረጉን ጠቁመዋል።
ድንገተኛ ወረርሽኝ ቢከሰት ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚችሉ የባለሙያ ቡድኖች በየደረጃው መዋቀራቸውን የገለጹት ኃላፊው፤ ከዝናብ ጋር ተያይዞ ሊከሰቱ የሚችሉ በሽታዎችን ለመቆጣጠር የቅኝት ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም አክለዋል።
በተጨማሪም የትንኝ መራቢያ ቦታዎችን ለማጥፋት የሚያስችሉ የጸረ-ትንኝ ኬሚካል ርጭትና የቆሙ ውኃዎችን በዘመቻ የማስወገድ ሥራ እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። የጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችም በቤት ለቤት ልየታና ግንዛቤ በመፍጠር ተግባር ላይ መሠማራታቸውን ዶ/ር አብዲ ገልጸዋል።
ኅብረተሰቡ በቤቱና በዙሪያው የሚገኙ የውኃ መቆያዎችን በማጽዳት የትንኝ መራቢያ እንዳይሆኑ ጥንቃቄ እንዲያደርግ፣ ውኃን አፍልቶና አክሞ እንዲጠቀም እንዲሁም በኬሚካል የተነከሩ አጎበሮችን በአግባቡ እንዲጠቀም ኃላፊው አሳስበዋል።
ማንኛውም ሰው ትኩሳት፣ ራስ ምታት ወይም የተቅማጥ ምልክቶች ሲታዩበት በአቅራቢያው ወደሚገኝ የጤና ተቋም በአፋጣኝ መሄድ እንዳለበትም ተገልጿል።
በመጨረሻም ዶክተር አብዲ አሚን የጤናው ዘርፍ የሚሠራቸውን የመከላከል ሥራዎች ውጤታማ ለማድረግ የኅብረተሰቡ ተሳትፎና የጥንቃቄ መልዕክቶችን ተግባራዊ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን በመግለጽ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
ዘጋቢ፦ ቤተልሔም ደሴ
08/08/18