
30/07/2025
እምነት ማጉደል ወንጀል የሚያስከትለው የወንጀል ተጠያቂነት
መግቢያ
እምነት ማጉደል በንብረት ላይ ከሚፈፀሙ ወንጀሎች መካከል አንዱ ሲሆን በ1996 ዓ.ም በወጣው የኢ.ፌ.ድ.ሪ የወንጀል ህግ እንዲሁም በሙስና ወንጀሎች አዋጅ ቁጥር 881/2007 መሰረት የወንጀል ተጠያቂነት የሚስከትል ነው፡፡ በዚህ ጽሁፍ የእምነት ማጉደል ወንጀልን ምንነት እና የሚያስከትለውን የወንጀል ተጠያቂነት በአጭሩ እንመለከታለን።
የእምነት ማጉደል ወንጀል ምንነት
በ1996 ዓ.ም በወጣው የወንጀል ህግ አንቀጽ 675 መሰረት እምነት ማጉደል ወንጀል ማለት ተገቢ ያልሆነ ብልጽግና ለራስ ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ የሌላ ሰው የሆነውና ለአንድ ለተወሰነ አገልግሎት ወይም በአደራ የተሰጠን ዋጋ ያለውን ነገር ወይም ጥሬ ገንዘብ በሙሉ ወይም በከፊል ለራስ ወይም ለሌላ ሰው ማድረግ፣ መውሰድ፣ ማስወሰድ፣ መሰወር ወይም ለራስ ወይም ለሌላ ሰው አገልግሎት ማዋል ወይም ይህንን የመሰለ ማንኛውንም አድራጎት መፈፀም ነው።
በዚህ መሰረት የእምነት ማጉደል ወንጀል ተፈፅሟል ለማለት
• ድርጊቱ የተፈፀመው ለራስ ወይም ለሌላ ሰው ተገቢ ያልሆነ ብልፅግና ለማግኘት ወይም ለማስገኘት በማሰብ መሆኑ፣
• ድርጊቱ የተፈፀመው የሌላ ሰው በሆነ እና ለተወሰነ አገልግሎት ወይም በአደራ በተሰጠ ዋጋ ያለው ነገር ወይም ጥሬ ገንዘብ ላይ መሆኑ፣
• በአደራ የተሰጠውን ንብረት ወይም ገንዘብ በከፊል ወይም በሙሉ ለራስ ወይም ለሌላ ሰው መደረጉ መረጋገጥ አለበት።
ከላይ በተገለፀው አንቀጽ ስር የተቀመጡት ፍሬ ነገሮች ተሟልተው የእምነት ማጉደል ወንጀል ተፈፅሞ በተገኘ ጊዜ እንደነገሩ ሁኔታ በቀላል እስራት ወይም ከአምስት አመት በማይበልጥ ፅኑ እስራት የሚያስቀጣ ይሆናል።
ከባድ እምነት ማጉደል
በወንጀል ህጉ አንቀጽ 675 ላይ የተቀመጡት ፍሬ ነገሮች እንዳሉ ሆነው ወንጀል ፈፃሚው የመንግስት ወይም የህዝባዊ ድርጅት ሰራተኛ ሆኖ ወንጀሉ የተሰራው በመንግስት ወይም በህዝባዊ ድርጅት ለአንድ ለተወሰነ አገልግሎት ወይም አደራ በተሰጠው ዋጋ ያለው ነገር ወይም ጥሬ ገንዘብ ላይ እንደሆነ በሙስና ወንጀሎች አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀፅ 31 መሰረት ከባድ እምነት ማጉደል በመሆኑ በሙስና ወንጀል ተጠያቂ ይሆናል። በተጠቀሰው አኳኋን ወንጀሉ ተፈፅሞ ከተገኘ ወንጀል ፈፃሚው ከሶስት አመት እስከ ሰባት አመት በሚደርስ ፅኑ እሰራት እና ከብር 10,000 (አስር ሺ) እስከ 50,000 (ሃምሳ ሺ) በሚደርስ መቀጮ እንደሚቀጣ በአዋጁ አንቀጽ 31(1) ላይ በግልጽ ተደንግጎ ይገኛል። የተገኘው ጥቅም ከፍተኛነት፣ የጥፋተኛው ስልጣን ወይም የሀላፊነት ደረጃ ወይም በመንግስት፣ በህዝባዊ ድርጅት፣ በህዝብ ወይም በግለሰብ ጥቅም ላይ ያደረሰው ጉዳት ከፍተኛነት በአዋጁ አንቀጽ 31(2) መሰረት ቅጣቱን የሚያከብደው ሲሆን ይህም ከሰባት አመት እስከ ሃያ አምስት አመት በሚደርስ ፅኑ እስራት እና ከብር 50,000 (ሃምሳ ሺ) እስከ 100,000 (አንድ መቶ ሺ) በሚደርስ መቀጮ የሚያስቀጣ ነው።
በተጨማሪም የወንጀል ህጉ አንቀጽ 676(2) መሰረት
• ወንጀሉን የፈፀመው በሞግዚት ወይም በንብረት ጠባቂ፣ በሂሳብ አጣሪ፣ በህግ ወይም በገንዘብ አማካሪ፣ በወኪል፣ በጠበቃ፣ በንብረት አስተዳዳሪ ወይም በሥራው ወይም በተሰጠው ሀላፊነት ምክንያት ንብረቱ እጁ በገባ ማንኛውም ሌላ ሰው እንደሆነ
• በእምነት በተቀበለው ሰነድ ላይ ሰጭውን ባለእዳ የሚያደርግ ግዴታ አስመስሎ በመጻፍ ወይም የገንዘብ መቀበያ ሰነድ በማስመሰል ወይም በፈራሚው ንብረት ላይ ጉዳት በሚያደርስ በማናቸውም ሌላ አይነት አድራጎት እንደሆነ ወይም
• ወንጀሉን የፈፀመው ስለ ገንዘብ መሰብሰብ ለህዝብ ጥሪ በሚያደርግ ሰው ሆኖ ለራሱ ወይም ለአንድ የንግድ ማህበር ወይም ለባንክ ወይም ለሌላ ድርጅት ጥቅም ሲል ገንዘብ ወይም ዋጋ ያላቸውን ነገሮች በሚሰበስብ ሰው እንደሆነ ወንጀሉን ከባድ እምነት ማጉደል የሚሆን ሲሆን ፈፃሚውም ከአንድ አመት በማያንስ ቀላል እስራት ወይም ከአስራ አምስት አመት በማይበልጥ ፅኑ እስራት የሚቀጣ ይሆናል።
ማጠቃለያ
የእምነት ማጉደል ወንጀል ምንነት ከላይ የተገለፀው ሲሆን ለተወሰነ አገልግሎት ወይም በአደራ ዋጋ ያለውን ነገር ወይም ጥሬ ገንዘብ የሚቀበል ማንኛውም ሰው የተቀበለውን ንብረት ለታለመለት አላማ በማዋል ከወንጀል ተጠያቂነት እራሱን ሊጠብቅ ይገባል፡፡
በንቃተ ህግ ትምህርትና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ
የፍትህ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን ይቀላቀሉ
Facebook
https://www.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_externa