18/03/2026
በአዲስ አበባ ከተማ ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ ብቻ 5 ሺሕ 805 ፍቺዎች መመዝገባቸውን የከተማዋ የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ አስታወቀ። ይህ ቁጥር ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የሁለት ሺህ ብልጫ አሳይቷል።
በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ 19 ሺሕ 800 ጋብቻዎች የተመዘገቡ ሲሆን፣ ከፍቺዎቹ መካከል 1 ሺሕ 750 ያህሉ በሕጉ መሠረት ፍቺው በተፈጸመ በ30 ቀናት ውስጥ የተመዘገቡ ናቸው። ቀሪዎቹ ፍቺዎች ለተለያዩ ማኅበራዊ አገልግሎቶች እንደ ቅድመ ሁኔታ በመጠየቃቸው ምክንያት ዘግይተው የተመዘገቡ መሆናቸውን የኤጀንሲው ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ጥጋቡ ሹመይ ገልጸዋል።
የፍቺ መንስኤዎችና ማኅበራዊ ቀውሶች፣
የሕግና ማኅበራዊ ጉዳይ አማካሪዋ ወ/ሪት መቅደስ አስፋው እንደገለጹት፣ በትዳር ውስጥ የሚከሰቱ ግጭቶች ድንገተኛ አይደሉም። ይልቁንም "ይስተካከላሉ" በሚል ቸልተኝነት የታለፉ ጥቃቅን ጉዳዮች ተደራርበው ለፍቺ ያበቃሉ።
ፍቺ በቤተሰብና በሀገር ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖ ከፍተኛ መሆኑን የጠቀሱት አማካሪዋ፣ በተለይም በልጆች ላይ የሚከተሉትን ችግሮች ያስከትላል ብለዋል፦
* የማንነት ጥያቄ፦ ሕፃናት የወላጆቻቸውን አለመግባባት እያዩ ማደጋቸው በራሳቸው ላይ ጥርጣሬ እንዲያድርባቸው ያደርጋል።
* ግለኝነት፦ ልጆች ስለ ማኅበረሰብ ከማሰብ ይልቅ ራሳቸውን በማዳን ስሜት ውስጥ እንዲወድቁና ለሀገር ብልጽግና እንቅፋት እንዲሆኑ ያደርጋል።
* ሥነ-ልቦናዊ ቀውስ፦ ጤናማ ያልሆነ የቤተሰብ መዋቅር ለወደፊቱ ጤናማ ዜጋ እንዳይፈጠር ያደርጋል።
መፍትሔው ምንድን ነው?
የፍቺ ቁጥርን ለመቀነስና የልጆችን ሥነ-ልቦና ለመጠበቅ ዋነኛው መፍትሔ የቅድመ ጋብቻ ዝግጅት መሆኑ ተጠቁሟል። ተጋቢዎች ወደ ትዳር ከመግባታቸው በፊት፦
* ለኃላፊነት ዝግጁ መሆናቸውን ማረጋገጥ።
* የግልና የአካባቢ ተጽዕኖዎችን አስቀድሞ መለየት።
* በትዳር ውስጥ ለሚገጥሙ ፈተናዎች በቂ ግንዛቤ መያዝ እንዳለባቸው ተመክሯል።