22/12/2025
🛑 ልጅ ከመውለድህ በፊት ራስህን ፈውስ!
▫️ከወለድክም ትራውማህን አታስተላልፍ!
በየሶሻል ሚዲያው፣ በየታክሲውና በየአካባቢው ጩኸቱ ይሰማሃል?
"ትዳር በረከት አጣ"፣ "ፍቺ በዛ"፣ "የዘንድሮ ልጆች አይሰሙም/ባለጌ ሆኑ"፣ "ማህበረሰቡ ተበላሸ፣ ፍቅር ጠፋ..." የሚለው እሮሮ በዝቷል። እውነት ነው፤ ብዙ ነገሮች ተበላሽተዋል።
ነገር ግን የምንሰጠው ምክንያትና መፍትሄ ላይ ትልቅ ስህተት አለ።
ብዙዎቻችን "ልጅ ሲመጣ ትዳሩ ይስተካከላል" ወይም "ልጅ ለቤቱ ድምቀት ነው" በሚል የራሳችንን ባዶነት ለመሙላት ብቻ እንወልዳለን። እውነታው ግን የመጣው ልጅ የትዳር ማስተካከያ ወይም የብቸኝነት ማስታገሻ ኪኒን አይደለም።
በኢትዮጵያዊ የልጅ አስተዳደግ ልማዳችን ውስጥ ብዙ ያልተሰሩ የቤት ስራዎች አሉ። ዛሬ የምናየው "የማህበረሰብ መበላሸት" የድሮ "የአስተዳደግ ክፍተት" ውጤት ነው። ይህ ክፍተት በብዙ ምክንያቶች የመጣ ነው። (ምክንያቶቹን ሌላ ጊዜ እንመለስባቸዋለን።)
ለምን?
ጥናቶችስ ምን ይላሉ?
ይህ የምናወራው ጉዳይ ከባዶ ሜዳ የተነሳ ስሜት አይደለም። በዓለም አቀፍ ደረጃ የተደረጉ ግዙፍ ሳይንሳዊ ጥናቶች (Meta-Analyses on Adverse Childhood Experiences - ACEs) የሚያረጋግጡት አስደንጋጭ እውነታ አለ።
በተለያዩ ሀገራት የተደረጉ በርካታ ጥናቶችን ያጠቃለለ ሜታ-አናሊሲስ እንደሚያሳየው፤ በልጅነታቸው የስነ-ልቦና ቁስል፣ የአካል መቁሰል፣ ወይም የቤተሰብ ፍቅር ማጣት (Neglect) ያጋጠማቸው ልጆች፣ ወደ አዋቂነት ሲሸጋገሩ፡-
1. ለአዕምሮ ጤና ቀውስ (ድብርት፣ ጭንቀት፣ ራስን ማጥፋት) የመጋለጥ እድላቸው እጅግ ከፍተኛ ነው።
2. ለሱስ እና ለአደገኛ ባህሪያት ይጋለጣሉ (ይህ ዛሬ የምናየውን የወጣቶች "መበላሸት" የምንለውን ያጠቃልላል)።
3. ጤናማ ትዳር እና ማህበራዊ ግንኙነት መመስረት ይቸገራሉ። ምክንያቱም ያላገኙትን ፍቅርና መተማመን መስጠት አይችሉም።
ስለዚህም፣
1. ያልዳነ ቁስል (Trauma) ታቅፎ ልጅ መውለድ ምን ያስከትላል?
ብዙ ወላጆች ከልጅነታቸው የመጣ ያልዳነ የሥነ-ልቦና ቁስል (Trauma) አለባቸው። በልጅነትህ ተገፍተህ፣ ተረግጠህ ወይም ፍቅር ተነፍገህ ካደክና ይሄንን ሳታክም አንተም ልጅ ከወለድክ፤ ያንኑ ህመም ሳታውቀው ለልጅህ ታወርሳለህ። የምትጮኸው፣ የምትናደደው፣ ወይም ልጁን የምትቀጣው ልጁ ስላጠፋ ብቻ ሳይሆን ያንተ የውስጥ ህመም ስለተነካ ነው።
2. ዲሲፕሊን ወይስ የበቀል እርምጃ?
ልጆች ሲያጠፉ የምንወስደው እርምጃ ማረም ወይስ መቅጣት? በኢትዮጵያ ብዙ ቤተሰቦች ውስጥ "ዲሲፕሊን/ሥነሥርዓት" ማለት ማስፈራራት፣ መደብደብና ማሸማቀቅ ነው። ይህ ደግሞ ነገ እልህ የሚጋባ፣ ለራሱ ክብር የሌለው፣ በትንሽ ነገር ትዳሩን የሚያፈርስና ከሰው ጋር መኖር የማይችል "የቆሰለ ትውልድ" ይፈጥራል።
3. የትኩረት ማነስ (Emotional Neglect)፣
ልጆች ከምግብና ልብስ በላይ "መደመጥን" ይፈልጋሉ። እያንዳንዳቸው ዛሬ የምናማርርባቸው ወጣቶች ቢጠየቁ፤ በልጅነታቸው "አባቴ አይሰማኝም"፣ "እናቴ አትረዳኝም" ብለው ያደጉ ናቸው። ቤቱ ውስጥ ያጣውን ፍቅርና ትኩረት ፍለጋ ወደ ውጭ ሲወጣ ነው ማህበረሰቡ "ተበላሸ/ ስድ ሆነ" የሚለው። ልጅ ሲበላሽ ተጠያቂው አካባቢው ወይም ሰፈሩ ብቻ ሳይሆን፤ የልጁን ስሜት ያላደመጠው ቤተሰብም ጭምር ነው።
ወዳጄ!
ልጅ መውለድ ቀላል ነው፤ "ሰው መፍጠር" ግን ከባድ ነው። ያልዳነ ሰው ሌላ የቆሰለ ሰው ይፈጥራል። ትዳር የሚፈርሰው፣ ማህበረሰቡ የሚታወከው እኮ ሰዎች በልጅነታቸው ያላገኙትን ፍቅርና ክብር በጉልበት ለማግኘት ሲሞክሩ ነው።
ስለዚህ ሰንሰለቱን እንበጥስ!
▫️ከመውለድህ በፊት ራስህን ፈትሽ።
▫️ያለፈ ህመምህን አክም።
▫️ልጅን "ንብረትህ" ሳይሆን "አደራህ" አድርገህ ተቀበል።
▫️ጊዜ ስጠው፣ አድምጠው፣ ቅረበው።
የተሻለች ሀገር፣ የሰከነ ትዳርና መልካም ትውልድ የሚገኘው ዛሬ በምንወልደው ልጅ ላይ በምንሰራው የሥነ-ልቦና ፈውስ ነው።
ለልጅህ የምታወርሰው ምርጥ ቅርስ "የዳነና ጤናማ አዕምሮ ያለው ወላጅ" መሆንህን ነው።
ይህ መልእክት ለሌሎች እንዲደርስ ሼር በማድረግ የድርሻዎን ይወጡ!
ማሳሰቢያ⁉️
ይህ በጥናት ላይ የተመሰረተ እና በየትኛውም አገር ላይ የሚሰራ ነው። ያደጉ አገራትም ከትራውማ ነጻ አለመሆናቸውን እና ጥናቱ በእነሱ ላይ እንደተሰራም ጭምር ልብ ማለት ያስፈልጋል። በአሜሪካ እንኳን 64% የሚሆኑት አዋቂ ሰዎች ከ18 ዓመታቸው በፊት ቢያንስ አንድ ጊዜ አጋጥሟቸው ያውቃል። ከ6 ሰዎች አንዱ ደግሞ 4 እና ከዚያ በላይ ትራውማዎች ደርሰውበታል።