03/02/2026
" ዜሮ... " ይሁንልን!!!!
ከሠዉ ቤት እንጀራ አልጫ መረቁ
የእናት እጅ ይጥማል ዘንጋዳዉ ደረቁ
እናት ለምን ትሙት ትሂድ አጎንብሳ
የምታሳድግ ናት በችግር ተጠብሳ...
(ይቀጥላል)
ከላይ ያለዉን ስንኝ የወሰድኩት አንጋፋዉ ድምጻዊ አለማየሁ እሸቴ በ1962 ዓ.ም ከተጫወተዉ ግሩም ዜማ ላይ ነዉ።
በምድር ላይ ከእናት ሞት በላይ መራር ሀዘን የለም ! ሞት የማይቀር የተፈጥሮ ግዴታ ቢሆንም ድምጻዊዉ እንዳለዉ
እናት ዝንተ-ዓለም አብራን ብትኖር የሁላችንም ምኞት ነዉ!
አይሆንም እንጂ ሎሬት ፀጋዬ " ሞትም ይሙት ፤ የት አባቱ" ያለዉ ቢሆን ሠርግና ምላሽ ነበር። የባለቅኔዉ ሀሳብ እንደተጠበቀ ሆኖ... የእናት ሞትን ማዳን እየተቻለ ህይወት ሲያልፍ ....ልብ ይሰብራል...! ቅስም ያደቃል ...! በተለይ ልትወልድ ሄዳ እናት ስትሞት...!!! አስባችሁታል ....
የመንደርደሪያዉ ሀሳብ ወደ ቀኝ ወደ ግራ ሳይል የሚያርፈዉ በሆስፒታላችን በዛሬዉ ዕለት በድምቀት የተከበረዉን የጤናማ እናትነት ወርን ይመለከታል።
" ፈጠራ እና ዘላቂ ፋይናንስ ለጤናማ እናትነት " በሚል መሪ ቃል በተሰናዳዉ መርሃ-ግብር ላይ ዋና ስራ አስኪያጁ ዶ/ር ታሪኩ ደሬሳ ካደረጉት ንግግር ዉስጥ የሚከተለዉን አጽንኦት እሰጣለሁ!
" በሀገር አቀፍም ይሁን በከተማ ደረጃ በርካታ እናቶችን በማዋለድ ቅድሚያዉን እንይዛለን። በዓመት 10,000 ገደማ እናቶች እኛ ጋር ወልደዉ ይስማሉ። "
( ስራ እስኪያጁ ቀጥለዋል...)
"እንደ ጋንዲ አንድ መፈክር አለን ...እሱም የእናት እና ህጻናት የሞት ቁጥርን መቀነስ ሳይሆን ዜሮ ማድረግ ነዉ! አንድ እናት እኛ ጋር ስትሞት ቁጥሩ ለኛ 1 ብቻ ነዉ ፣ ለቤተሰቦቿ ግን 100% ጥልቅ ሀዘን ነዉ...በዚህ መነሻነት ግባችንን ለማሳካት የአገልግሎት ጥራትን በተመለከተ ቀን ከ ሌት እየሠራን እንገኛለን ...ዉጥናችን እንደሚሳካም እርግጠኛ ነኝ..." ብለዋል።
ወ/ሮ አንጋቱ መሀመድ የከተማችንን ጤና ቢሮ በምክትልነት ይመራሉ። " አናቶች ያለ ምንም ችግር በሰላም ተገላግለዉ እንዲያዩ በሙያቸዉ እያገለገሉ ላሉ የጤና ባለሙያዎች ምስጋና አቀርባለሁ ። ....እንደ ሀገር የእናቶች እና ህፃናትን ሞት ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ መቀነሳችንን የአለም ጤና ድርጅት ሳይቀር እዉቅና ሰጥቶናል። ...እኛ ግን አላማችን በወሊድ ምክንያት የሚመጣን የእናቶች እና ህጻናትን ሞት ከነጭራሹ ማስቀረት ነዉ" ብለዉናል።
በጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ደ.ኤ.ታ አማካሪዉ አቶ ዬናስ ዙላ
ከተናገሩት መሀከል " በሀገራችን የእናቶች እና ህጻናት የሞት ምጣኔ መቀነሱ ለጉዳዩ ትኩረት እንደተሠጠ ማሳያ ነዉ " ያሉትን አስምሬበታለሁ።
በመቀጠልም ከተለያዩ ተቋማት በመጡ ባለሙያዎች የፓናል ዉይይት ተደርጎ ፣ የእናቶች ጤና ላይ ያተኮረ አዉደ-ርዕይ በታዳሚዎቹ ተጎብኝቶ የመርሃ-ግብሩ ማሳረጊያ የነበረዉ ክብርት ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ ሆስፒታሉን በጎበኙበት ወቅት " ቢሆን ጥሩ ነዉ ...." ብለዉ የሰጡትን አስተያየት ተከትሎ የተሠሩ የማሻሻያ ስራዎች ተጎብኝተዉ ይሁንታን አግኝተዋል። ጎን ለጎንም በህክምና ላይ ለማገኙ እናቶች የተለያዩ ስጦታዎች ተበርክቶላቸዉ እንግዶቹ ተሸኝተዋል።
26/05/2018