
16/06/2025
ኪነጥበብ ለተረጋጋ ሰላምና ለተጠናከረ ባህል ግንባታ
አዲስ አበባ ሰኔ 9/2017 ዓ.ም (አማ/አእ/ስፔ/ሆ/ል) ከሰኔ 7-9/2017 ዓ.ም ድረስ በአዲስ አበባ በመስቀል አደባባይ በተካሄደው የ16ኛው ከተማ አቀፍ አዲስ የኪነጥበብ ፌስቲቫል ላይ የአማኑኤል አእምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የኪነጥበብ ስራዎችን በፌስቲቫሉ ላይ ማቅረብ ችሏል፡፡
ሆስፒታሉ የኪነጥበብ ስራዎቹን ለእይታ ያቀረበው በሆስፒታሉ ውስጥ አንዱ የህክምናው አካል በመሆን እየተሰጠ የሚገኘው የኪነጥበብ ህክምና (Art Therapy) በሚሰጠው የተሃድሶ ህክምና አማካኝነት የተሃድሶ ህክምና አገልግሎት የሚሰጣቸው ታካሚዎች የአእምሮ ውጤት የሆኑትን የጥበብ ስራዎችን ነው፡፡
የሆስፒታሉ የአመራር አካላትም በፌስቲቫሉ በመገኘት የኪነጥበብ ስራዎችን ተዘዋውረው በጎበኙበት ወቅት ከሌሎች አጋር የኪነጥበብ ተቋማት ጋር በጋራ ለመስራትና ተሞክሯቸውንም ለመካፈል እድል ያገኙበት አጋጣሚም ነበር፡፡
ከፌስቲቫሉ ባሻገር ኪነጥበብና የአእምሮ ጤናን ስናነሳ የሰው ልጅ በግማሽ ስውር የአእምሮ ሰርጡ ውስጥ ተወሽቆ የሚያሰቃየውን ስሜት ወደ ገሃዱ አለም አውጥቶና አሽቀንጥሮ የሚገላገልበት መንገድ ቢኖር አንዱና ዋነኛው ጥበብ ነው፡፡
በዚህም የአእምሮ ጤና ጉዳይ በብዙ መልኩ ከፈጠራ ጋር የተሳሰረ ነው፡፡ በአንድ ወቅት ዶ/ር ዳዊት አሰፋ (የቀድሞ የሆስፒታሉ ስራ አስኪያጅ የነበሩ) በአማኑኤል አእምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ክትትል እያደረገ ከነበረ ተገልጋይ የሰማሁት ነው ብለው በብዕራቸው ካጋሩን ነጥብ ስንነሳ አእምሮውን የሚታመም አእምሮ ያለው ነው በማለት ነው ለዚህም ተገልጋዩ ርዕቱ ሃሳብ ሲያቀርብ ደሃ ይከስራል ኪሳራ የሚደርስበት ሃብታም ነው የሌለው ሊከስር አይችልም በማለት ነው፡፡ የአእምሮ ችግር የገጠማቸው የአእምሮ ህሙማን ሃሳባቸውን፤ ስሜታቸውን እና አጠቃላይ ሰውነታቸው ሙሉ በሙሉ የጠፋ ወይንም እንዳይመለስ ሆኖ የተበላሸ ለሚመስለን ሰዎች ይህ መልካም ትምህርት ነው፡፡ በዚህም የኪነጥበብ ህክምና የአማኑኤል አእምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል አንዱ የህክምና ዘርፍ ከሆነ በርካታ ጊዜያት ተቆጥረዋል፡፡
በሌላ በኩል ኪነጥበብን በተመለከተ ፕ/ር መስፍን አርዓያ በብዕራቸው ሲያብራሩ አእምሮ ከጥበብ ይቀድማል የኋለኛዋ ደግሞ ያለፊተኛው አትሆንም ጥበብ ተጠንስሳ የምታድገው በአእምሮ ነው፡፡ ጥበብ በድምፅ፤ በስዕል፤በቅርፅ፤ በፅሁፍና በእንቅስቃሴ በተለያየ መንገድ ይገለፃል፡፡ ማዘን፤መከፋት፤መቆጣት፤መፍራት፤ መደሰትም ሆነ መርካት በተለያየ ሁኔታ መግለፅና ከድርጊቱ በኋላም ማስቀረት ይቻላል ይሉናል፡፡
ጥበብ ለሌሎች ማሳወቂያ ብቻ ሳይሆን ከሁሉም በላይ ከራስ መታረቂያ፤ ብሎም አእምሮን ማፅጃ፤ መታከሚያና መዳኛ መሳሪያ ነች