08/03/2026
ይህ ታሪካዊ ድል የተቋሙ አመራርና ሰራተኞች ለጤና ስርዓቱ መሻሻል ያበረከቱት የላቀ ጥረት ውጤት ነው - ዶ/ር አምባቸው ዱማ
አርባምንጭ፡ የካቲት 29/2018 ዓ.ም (የጋሞ ዞን ጤና መምሪያ) )
የአርባ ምንጭ አጠቃላይ ሆስፒታል በሀገር አቀፍ ደረጃ በተደረገ የሆስፒታሎች የጥራትና የአገልግሎት አሰጣጥ ግምገማ 3ኛ ደረጃን በመያዝ የሁለት ሚሊዮን ብር ተሸላሚ ሆኗል።
ለልኡክ ቡድኑ በተደረገው ደማቅ የአቀባበል ስነስርዓት ላይ ተገኝተው መልእክት ያስተላለፉት የአርባምንጭ አጠቃላይ ሆስፒታል ዋና ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር አምባቸው ዱማ ይህ ታሪካዊ ድል የተቋሙ አመራርና ሰራተኞች ለጤና ስርዓቱ መሻሻልና ለታካሚዎች ደህንነት ሌሊትና ቀን ያበረከቱት የላቀ ጥረት ውጤት መሆኑን ገልፀዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ በ90 ሆስፒታሎች መካከል በተደረገው ውድድር ሆስፒታሉ 3ኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ የሁሉም ባለድርሻ የነቃ ተሳትፎ መሆኑን ገልፀው ለተገኘው ውጤት አስተዋጽኦ ላደረጉ የክልልና የዞን ጤና መዋቅሮች፣ የቦርድ አባላትና ለመላው የሆስፒታሉ ባለሙያዎች ምስጋና አቅርበዋል።
አክለው ሆስፒታሉ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደግሞ የ1ኛ ደረጃን በመያዝ የክልሉና የዞኑ የኩራት ምንጭ መሆኑም ነው ዶ/ር አምባቸው የጠቆሙት።
የጋሞ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰይፉ ዋናቃ በበኩላቸው ይህ ውጤት ሆስፒታሉ በቀጣይ የተሻለ አገልግሎት እንዲሰጥ ለአመራሩና ሠራተኛው ትልቅ መነቃቃትን የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል።
ሆስፒታሉ ከጊዜ ወደ ጊዜ አዳዲስ አሰራሮችን ወደ ተግባር በመቀየር ለህብረተሰቡ ተደራሽ እየሆነ መምጣቱን ገልፀው ውጤቱ የመተባበር፣ የአንድነትና የላቀ ትጋት ምልክት መሆኑን ተናግረዋል።
የሆስፒታሉ ምክትል ዳይሬክተር ዶ/ር አዲሱ ተስፋዬ ሆስፒታሉ ቀደም ሲልም በተለያዩ ጊዜያት ተሸላሚ መሆኑን አስታውሰው፣ አሁን የተገኘውን ውጤት ለተሻለ ስራ የሚያነሳሳ ከመሆኑም በላይ ሆስፒታሉ በቀጣይ ይህንን ጥረቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል።
በመድረኩ የአርባምንጭ አጠቃላይ ሆስፒታል ዋና ስራ አስኪያጅ ዶ/ር አምባቸው ዱማ፣የጋሞ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰይፉ ዋናቃን ጨምሮ የሆስፒታሉ ሠራተኞች እንድሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል