19/11/2020
የነርቭ ዘንግ ክፍተት (Neural Tube Defect)
በዶ/ር ሄኖክ ዘውዱ
በአንዳንድ ጨቅላ ህፃናት ላይ በጀርባቸው ላይ ያበጠ ነገር እንዲሁም የጭንቅላታቸው መጠን በጣም የገዘፈ ሆኖ ሊታይ ይችላል፡፡ ይህም የነርቭ ዘንግ ክፍተት (Neural Tube Defect) ይባላል፡፡
ይህ ችግር ከላይኛው የአእምሮ ክፍል እስከ ታችኛው ህብለ ሰረሰር ድረስ የነርቭ ዘንግና መሸፈኛው የአፈጣጠር ችግር ሲኖርበት የሚከሰት ነው፡፡
እንደ የዓለም ጤና ድርጅት ግምት በየአመቱ እስከ 300ሺ በሚደርሱ ህፃናት ላይ ሞትና ጉዳትን የሚያስከትል ችግር ነው፡፡ በሀገራችንም የተከናወኑት ጥቂት ጥናቶች የችግሩን አሳሳቢነት ያመላከቱ ናቸው፡፡
መቀሌ ዩኒቨርሲቲ እ.ኤ.አ. ከ2016-2017 ድረስ ባካሄደው ጥናት በትግራይ ክልል ውስጥ ባሉ ሆስፒታሎች ከተወለዱ 10ሺ ህፃናት መካከል 131ዱ (131/10,000) ጨቅላ ህፃናት ከነርቭ ዘንግ ክፍተት ጋር መወለዳቸውን አስረድቷል፡፡
በተመሳሳይ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በተደረገው ጥናት በአዲስ አበባ ባሉ 3 ሆስፒታሎች ውስጥ ከተወለዱ 10ሺ ህፃናት መካከል 126ቱ (126/10,000) ጨቅላ ህፃናት የነርቭ ዘንግ ክፍተት እንዳለባቸው ተረጋግጧል፡፡
የነርቭ ዘንግ ክፍተት ያለባቸው ህፃናት ተያያዥ የጭንቅላት መጠን በአእምሮ ፈሳሽ መሞላትና መጠኑ መጨመር (hydrocephalus)፣ የእግር አለመንቀሳቀስ መጣመምና ውስጣዊ አካላዊ ችግሮች ሊኖሩባቸው ይችላሉ፡፡
ለነርቭ ዘንግ ክፍተት አጋላጭ የሆኑ ነገሮች
-የፎሊክ አሲድ እጥረት
- እናትየው የምትወስዳቸው መድኃኒቶች የፎሊክ አሲድን የሚፃረሩ ከሆኑ
ለምሳሌ የሚጥል ህመም መድኃኒቶች
- ከዚህ በፊት በተመሳሳይ ችግር ያለው የወለደች እናት በተከታታይ በዚሁ ችግር የተጠቃ ልጅ የመውለድ እድሏ ከፍተኛ መሆን ከመንስኤዎቹ መካከል ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
የነርቭ ዘንግ ክፍተት ያለባቸውን ህፃናት ለማከም ከፍተኛ የሆነ ወጪ ይጠይቃል፡፡ በተጨማሪም የብዙ ባለሙያዎችን ርብርብ የሚፈልግና ፈታኝ ሲሆን የህክምና ውጤቱም በአብዛኛው ጥሩ አይደለም፡፡ በመሆኑም በዋነኝነት የእርጉዝ እናት የፎሊክ አሲድ አጠቃቀምን በማስተካከል መከላከል ላይ ማተኮር ያስፈልጋል፡፡
በፎሊክ አሲድ የበለፀጉ ምግቦችን ለመውለድ የሚያስችል የእድሜ ክልል ውስጥ ያሉ ሴቶች አብዝተው መመገብ አለባቸው፡፡
እነዚህም በፎሊክ አሲድ የበለፀጉ ምግቦች አትክልት ፣ፍራፍሬና የእንሰሳት ተዋፅኦ ናቸው፡፡
• ፓፓያ፣ አቮካዶ፣ብርቱካን
• ቀይስር፣ አበባ ጎመን
• ባቄላ፣አተር
• እንቁላል እና የጉበት ስጋ በፎሊክ አሲድ የበለፀጉ ናቸው ::
ለማርገዝ ያሰበች እናት ቅድመ እርግዝና ምክክር በማድረግ ከመጀመሪያው የእርግዝና ቀን ጀምሮ ለ3 ወራት የፎሊክ አሲድ እንክብሎችን መውሰድ ይኖርባታል፡፡ በተለይም ከዚህ በፊት ተመሳሳይ ችግር ያለው ህፃን የወለደች እናት ከፍ ባለ መጠን መውሰድ ይጠበቅባታል፡፡
እንደ ችግሩ አሳሳቢነት በማህበረሰብና በአገር አቀፍ ደረጃ ስለነርቭ ዘንግ ክፍተት ግንዛቤ እና ስለፎሊክ አሲድ ጥቅም ብዙ አልተሰራም፡፡ ይህም የዚህ ችግር ተጠቂዎች ከእለት እለት ከፍ ባለ ቁጥር እንዲታዩ አድርጓል፡፡ በመሆኑም በማህበረሰብ ደረጃ የፎሊክ አሲድ ጥቅምና የነርቭ ዘንግ ክፍተት የመከላከል እውቀት ማስፋፋት በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡
picture -wikipedia