03/17/2026
ከ 6.5 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የሕክምና አገልግሎት ተሰጠ
4ኛው ዓመታዊው "መጻጉዕን በመቄዶንያ" ነጻ የሕክምና አገልግሎት ተጠናቀቀ።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሕክምና ማኅበር በየዓመቱ የሚያደርገውን "መጻጉዕን በመቄዶንያ" ነጻ የሕክምና አገልግሎት ከየካቲት 29 እስከ መጋቢት 6 ለተከታታይ 8 ቀናት ሲያካሂድ ቆይቶ በተሳካ ሁኔታ ለማጠናቀቅ ቻለ።
በዚህ አገልግሎት ዘርፈ ብዙ የሕክምና አገልግሎት ከተሟላ ላቦራቶሪ እና ዲያግኖስቲክ ምርመራ ጋር ለመስጠት ተችሏል።
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የዓይን ሕክምና ክፍል ጋርም በመተባበር ለ 293 ሰዎች የዓይን ሕክምና የተሰጠ ሲሆን 54 የዓይን ሞራ ግርዶሽ (Cataract) ተጠቂ የሆኑ ታካሚዎች ተለይተው የቀዶ ሕክምና አገልግሎት ለመስጠት ተዘጋጅተዋል።
በጥርስ ሕክምና ባለሙያዎችም የተሟላ የጥርስ ሕክምና እንዲሁም የጥርስ ነቀላ (Dental extraction) ለማድረግ ተችሏል።
የልብ ሕክምና የሚያስፈልጋቸው ታካሚዎችም በልብ ሐኪሞች የተሟላ ሕክምና የተሰጣቸው ሲሆን 30 ታካሚዎች የልብ አልትራሳውንድ (Echocardiograph) እና ECG ተሰርቶላቸዋል።
በ ኢንተርናሽናል ክሊኒካል ላቦራቶሪ (ICL) ለ 1000 ታካሚዎች እንዲሁም በ አርሾ ሜዲካል ላቦራቶሪ ደግሞ ለ 150 ታካሚዎች የተሟላ የላቦራቶሪ ምርመራ ለማድረግ ተችሏል።
በተጨማሪም የፊዚዮቴራፒ እና የደረቅ መርፌ (Acupuncture) ሕክምና በባለሙያዎች የተሰጣቸውም ይገኙበታል።
በዚህ አገልግሎት ከተለያዩ የሕክምና ስፔሺያሊቲ እና የጤና ሙያ የተውጣጡ ከ160 በላይ ባለሙያዎች የተሳተፉ ሲሆን ከነዚህ ውስጥ 50 ስፔሺያሊስት፣ 6 ሰብስፔሺያሊስት ሐኪሞች ፣ 44 ጠቅላላ ሐኪሞች፣ 30 ነርሶች፣ 8 የጥርስ ሐኪሞች፣ ፋርማሲስቶች፣ ፊዚዮቴራፒስቶች፣ የስነእምሮ እና የማኀበረሰብ ጤና ባለሙያዎች እንዲሁም የላቦራቶሪ ቴክኒሺያኖች ይገኙበታል።
በ4ኛው ዓመታዊው "መጻጉዕን በመቄዶንያ" ነጻ የሕክምና አገልግሎት ባጠቃላይ 1070 ታካሚዎች የተለያዩ የሕክምና አገልግሎቶች ተጠቃሚ ሲሆኑ አጠቃላይ የተሰጠው የሕክምና አገልግሎትም በገንዘብ 6,502,115 ብር የሚገመት ነበር።
ለዚህ አገልግሎት መሳካት የረዳችሁንን የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የዓይን ሕክምና ክፍል ፣ ኢንተርናሽናል ክሊኒካል ላቦራቶሪ (International clinical laboratories)፣ አርሾ ሜዲካል ላቦራቶሪ (Arsho medical labratories P.L.C) ፣ ያኔት አጠቃላይ ሆስፒታል (Yanet General Hospital)፣ ዘውዲቱ መታሰቢያ ሆስፒታል (Zewditu Memorial Hospital)፣ ኦቶሪኖ ልዩ የአንገት በላይ ክሊኒክ (Otorino Ent Surgical Center) ፣ Badreg Pharmaceuticals እና ELPIS PHARMACEUTICALS በአገልግሎቱ ተጠቃሚ በሆኑት ወገኖቻችን ስም ለማመስገን እንወዳለን። ለጤና ባለሙያዎችም የምግብ አቅርቦት ድጋፍ ላደርጉልን ROMi Catering & Restaurant ከልብ እናመሰግናለን።
በዚህ የበጎ ፈቃድ የሕክምና አገልግሎት ለሳተፉት ባለሙያዎች እና ለአገልግሎቱ መሳካት ድጋፍ ላደረጉ ድርጅቶች የምስጋና ምስክር ወረቀት የተሰጠ ሲሆን፤ ጊዜያችሁን እና ሙያችሁን በነጻ ለወገናችሁ በመለገስ ለሰጣችሁት አገልግሎት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሕክምና ማኅበር ለማመስገን እንወዳለን።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሕክምና ማኅበር
“አክብሮትና ትህትናን የተላበሰ የጤና አገልግሎት ለሰው ልጆች በሙሉ”